ኢትዮጵያ አገራችን እያከተመ ባለው ምዕተ-ዓመት ሁለት የተለያዩ የማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፓለቲካዊ ለውጦችን አስተናግዳለች። የመጀመሪያው በ 1966 የፈነዳው አብዮትና ሶሻሊስታዊ እንቅስቃሴ ሲሆን፣ ሁለተኛው በክስተቱም ሆነ በውጤቱ እጅግ የተለየው ደግሞ ከ1983 ጀምሮ የተንሰራፋው የዘመነ መሳፍንት ተምሳሌት ወያኔ መራሹ ፓለቲካ ነው። ይህ በጎጥና በመንደረተኛነት ላይ የተመሠረተ አምባገነናዊ አገዛዝ እነሆ! ከ 25 አመታት ቆይታም በኋላ ኢትዮጵያን እያመሳት መሆኑ ብቻ ሳይሆን፣ ኅልውናዋን፣ ሉዓላዊነቷንና አንድነቷን አናግቷል። እያናጋም ነው።
በያዝነው ዓለም አቃፋዊነት ዘመን (ዘመነ ግሎባላዜሽን)፣ ዓለም እየጠበበችና አንድ መንደር እየሆነች መጥታለች። የአገራት ጂኦግራፊያዊና የኢኮኖሚ ክልል ሳይገድባቸው ባለሀብቶች ባሻቸው አሕጉር፣ አገርና ማናቸውም ሥፍራ መዋዕለ-ነዋያቸውን በማፍሰስ እራሳቸውን ጠቅመው ተቀባዩን አገርና ኅብረተሰብ እንዲጠቅሙ የሚበረታቱበት ውቅት ነው። ባለሙያዎች ዜግነትና ድንበር ሳያግዳቸው በሚፈለጉበት አገር ሁሉ ሙያቸውን እንዲያጋሩ በሩ በተከፈተበት ዘመን፣ ኢትዮጵያ ውስጥ የጎሳ ፓለቲካ ባሰመረው ክልል የተነሳ፣ የጋራ ደም የተከፈለባት ኢትዮጵያ የጋራ አገር ልትሆን አልቻለችም። ኢትዮጵያ ውስጥ፣ አገሪቱ የሁሉም ነገዶቿና ጎሣዎቿ አገር ሆና ሳለ፣ «የእኛና» «የእናንተ» እየተባለ በተከለለ የጎሳ አጥር፣ ሕዝቡ ተዘዋውሮ መሥራት እንዳይችል ገደብ ተጥሎበት ይገኛል። ነገዶችና ጎሣዎቻችን ጌጦቻችን መሆናቸው ቀርቶ፣ ለመከፋፈላችንና ለአንድነታችን መፍረክረክ ምክንያት እንዲሆኑ፣ በዘረኞች ቀመር ዞሪያ እየተሽከረከሩ ይገኛሉ። የውጭ ጻህፍት ሳይቀሩ «የነገዶች ሙዚየም» ብለው ያሞካሿት ኢትዮጵያ፣ በከፋፍለህ ግዛው የፓለቲካ ጦስ የእርስ በርስ ጦርነት መሻኮቻ መድረክ ሆናለች።
በቀዝቃዛው ጦርነት ማክተሚያ ወቅት፣ ኮሙኒዝምን ለመበቀል በዛቱት ምዕራባውያን ትከሻ፣ ኢትዮጵያን ለመቆጣጠር በለስ የቀናቸው የትግሬ-ወያኔዎች፣ ኢትዮጵያን ለመበታተን ሌት ተቀን እየሠሩ ለመሆናቸው ገሃድ ከሆነ ውሎ አድሯል። የኢትዮጵያን መሠረታዊና ጥንታዊ ዕሴቶች፣ የሕዝቧን ኅብረትና አብሮነት ለመናድ ሳይታክቱ ጠንክረው እየሠሩ ነው። ገና ከጽንሳቸው ጀምሮ፣ የጥፋት ዒላማቸው ያደረጉት ደግሞ የዐማራውን ማኅበረሰብ ነው። ዐማራውን ያለ ስሙ ስም ሰጥተው ፣ያለጥፋቱ ጥላሸት ቀብተው ፣ ብሔራዊ መለያ ደማቅ ቀለሙን አደብዝዘው ፣ አኩሪ ታሪካዊ ሚናውን አኮስሰው፣ ኮንነውና አጥላልተው ባምሳላቸው ለቀረጿቸው ጎጠኞች የጥቃት ዒላማ አድርገውታል። እነዚህ በኢትዮጵያ ሕዝብ ጫንቃ ላይ ያለፈቃዱ የተፈናጠጡ የወያኔ ዘረኛና ጠባብ ናዚዎች በውስጣቸው በተፈጠረ የበታችነትና የቅናት ስሜት የተነሳ፣ በሰነቁት ጥላቻ ይህንን ታላቅ፣ ታታሪና ለኢትዮጵያ የክፉ ቀን ዘብ የቆመንና ኢትዮጵያን እንዳገር ለማፅናት የታገለ ሕዝብ የዘር ማጽዳትና የዘር ማጥፋት ወንጀል ፈጽመውበታል። እየፈጸሙበትም ነው።
ጥቃቅን ችግሮችን በማጋነንና ልዩነት በመፍጠር አብሮ በኖረ ሕዝብ መካከል በቀላሉ የማይጠፋ እሳት ለኩሰዋል። ለጠባብ ዓላማቸው ስኬት ሲሉ፣ የጎሣ ፓለቲካን ከሚገባው በላይ አራግበውና አጡዘው፣ ከሁሉም በላይ የኢትዮጵያ ችግሮች ሁሉ መንስዔ የዐማራው ነገድ እንደሆነ ጧት ማታ በመልፈፍ፣ ልበወለድ ታሪኮችን በመፈብረክና ዕኩይ ፕሮፖጋንዳ በመንዛት መጠነ ሰፊ የዘር ማጥፋትና ማጽዳት ዘመቻ ከፍተውበታል።
ዐማራው በ18ኛው ክፍለ-ዘመን መባቻ ላይ፣ ኢትዮጵያን ሊቀራመቱ ከመጡ ቅኝ ገዢዎች መንጋጋ ሕይወቱን ገብሮ እንዳላዳናት፣ በ 21ኛ ክፍለ-ዘመን በዚችው አገር እንደባዕድና እንደወራሪ ተጨፈጨፈባት ። በተሰዋላት ኢትዮጵያ ውስጥ በግፍ ሕይዎቱን በግፈኞች ተነጠቀ። የዘር ማጽዳትና የዘር ማጥፋት ወንጀል ተፈጸመበት። ዘርን መርጦና ለይቶ የወል ወንጀል ሲፈጸም፣ ይህ በዐማራው ላይ የደረሰው በአገራችን ታሪክ ውስጥ የመጀመሪያው መሆኑ ነው።
አብዛኛው ዐማራ፣ በኑሮው ከማንኛውም የኢትዮጵያ ነገዶች ባነሰና በከፋ የድህነት አርንቋ ውስጥ መኖሩ በግልጽ እየታየ ፤ ገዛ፣ በዘበዘ ፣አደህየን ወዘተ በማለትና የሌለበትን ኃጢያት በመደርደር፣ ለዕኩይ ዓላማቸው የፕሮፓጋንዳ ፍጆታ ተጠቅመውበታል። ዐማራ የጎጠኝነትና የጠባብነት ስሜት ከቶ ኖሮት አያውቅም። ከማንኛውም ኢትዮጵያዊ ወገኑ ጋር ተጋብቶና ተስማምቶ የሚኖር ብቻ ሳይሆን፣ በሄደበት ቦታ ሁሉ፣ በታታሪነቱና ባለው የዳበረ ማኅበራዊ መስተጋብሩ ከማንኛውም ኢትዮጵያዊ ጋር እጅና ጓንት ሆኖ የሚኖር ማኅበረሰብ መሆኑ ማንም የሚያውቀው ነው። የጎጠኞች ፀረ-ዐማራ ርካሽ ቅስቀሳና መሠረተ ቢስ ክሳቸው፣ ተከላካይ ባለማግኘቱና ለዓመታትም በመደጋገሙ፣ ሌሎች ጠባቦችን ለመቀፍቀፍና ለማነሳሳት በቅቷል። በመሆኑም ዐማራው በተለያዩ የኢትዮጵያ ክፍሎች ዜግነቱን፣ ጥቅሙን፣ መብቱንና ክብሩን ብቻ ሳይሆን፣ ሰብአዊነቱንና ሕይዎቱንም ጭምር ተነጥቆ፣ቀሪው የሰቀቀን ሕይዎት በመግፋት ላይ ይገኛል።
ሞረሽ ወገኔ የዐማራ ድርጅት፣ የዐማራው ድምፅ ለመሆንና የገጠመውን መጠነ ሠፊ ችግር ለዓለም ማኅበረሰብ ለማመላከትና ለማሳወቅ ከተመሠረተ እነሆ ሦስት ዓመት ሊያስቆጥር ነው። በዚህ በአጭር ጊዜ ውስጥ የዐማራው ድምጽ ከመሆኑ በተጨማሪ፣ ዐማራው ምን እንደተፈጸመበት፣ ምን ሊፈጸምበት እንደታቀደና ያንዣበበትን ከፍተኛ የኅልውና አደጋ የቱን ያህል የከፋ እንደሆነ፣ እንዲገነዘብና እንዲያውቅ የበኩሉን ጥረት አድርጓል። አንቅቷል። ሞረሽ ሊያከናውናቸው ካቀዳቸው ግቦዎቹ ውስጥ አንዱ፣ ዐማራው ላይ የሚፈጸመውን የዘር ማጽዳትና የዘር ማጥፋት ወንጀል እየተከታተለ ማጋለጥና አስፈላጊው እርምጃ እንዲወሰድ የበኩሉን አስተዋጽኦ ማድረግ ነው። በዚም መሠረት ሞረሽ አንዱና ቀዳሚው ተግባሩ ያደረገው፣ ወያኔ ኢትዮጵያን ከተቆጣጠረበት ከዚያ ክፉ ቀን ጀምሮ፣ እስከ ዛሬ በዐማራው ነገድ ላይ የተከፈተውን መጠነ ሠፊ የማፈናቀልና የዘርማጥፋት ወንጀል ለማወቅና አስፈላጊውን እርምጃ ለመውሰድ እንዲቻል በመረጃ ላይ የተመሠረተ ጥናት ማካሄድ ነው። ይህንንም እንደሚያደርግ በተለያዩ መገናኛ ብዙኃን ማስተዋወቁ የሚታወስ ነው። ስለሆነም በሁሉም የኢትዮጵያ ክፍሎች በተለይም በዐማራው ላይ የዘር ማጽዳትና የዘር ማጥፋት ወንጀሎች የተፈጸሙባቸው አካባቢዎችን ያካተተ በተጨበጠ፣ ግልጽና አስተማማኝ መረጃዎች ላይ የተመሠረተውን ይህንን ጥናት አስጠንቶ ለራሱ የዐማራ ነገድ ተወላጆች፣ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶችና ለታሪክ ተመራማሪዎች የኅሊና ፍርድ አቅርቧል።
ጥናቱ የዐማራውን መጠነ ሠፊና በዝምታ ዕልቂት ለዓለም ይፋ ለማድረግ ተዘጋጅቷል። ጆሮ ያለው እንዲሰማ፣ ዓይን ያለው አጥርቶ እንዲያይ፣ ዐማራው በዚህ በጎጠኞች ዘመን የተደገሰለትን በአሉባልታ ሳይሆን፣ በተጨበጥና በሚዳሰስ መረጃ ቀርቦለታል። የዚህ ጥናት ውጤት ተነቦና ከንፈር ተመጦ እንደ አንድ የትራጄዲ ልበወለድ ለተወሰኑ ጊዜ ቆዝመው የሚተው አይደለም። ይልቁንም ማናቸውም ኢትዮጵያዊ በተለይም ዐማራው ኅብረተሰብ ከዚህ የከፋ ምንም እንደማይጠብቀው አውቆና ከራሱ በስተቀር ማንም ተገን እንደለሌው ተረድቶ፣ ለራሱ መቆም እንዳለበት እንዲገነዝብ የሚያግዝ ሁነኛ ዋቢ ታሪካዊ መረጃ ነው። ይህንን ግድያ ያቀነባበሩ፣ ያበረታቱና ቀጥታ ወንጀሉን የፈጸሙት ጎጠኞችና ጠባቦች የጊዜ ጉዳይ ነው እንጂ የሚጠየቁበት ጊዜ እሩቅ አይሆንም። የሞረሽ ወገኔ ፍላጎትም፣ የዚህ ጥናት የመጨረሻ ግብም ወንጀለኞችን ለሕግ ማቅረብ ነው።
የጥናቱ ዐብይ ዓላማ፦ ለአለፉት 25 ዓመታት በዐማራው ላይ የተፈጸመውን የዘር ማጥፋትና የዘር ማጽዳት ወንጀል የተጨበጠ መረጃ በማሰባሰብ፣ በአገር ውስጥም ሆነ በውጭ በሚኖሩ ወንጀለኞች ላይ ሕጋዊ እርምጃ እንዲወሰድ ማድረግ ሲሆን፣ የወንጀሉን ደረጃና መጠን ለኢትዮጵያ ሕዝብ በተለይም፣ ሰለባ ለሆነው ለዐማራው ኅብረተሰብ፣ ወንድምና እህቶቹ መርጠው ባልተወለዱበት ዘራቸው ተነቅሰውና ተፈርጀው የገጠማቸውን ሰቆቃ፣ እልቂትና ሰብአዊ ውርደት በትክክል እንዲያውቅ ማድረግ ነው። የጥናቱ ዓላማ በዝርዝር፦
■ ከ 1983 ዓ.ም ጀምሮ ያለቁና የተፈናቀሉ ዐማሮችን መጠን ለማወቅ፣ እንዲሁም የወያኔ የጎሳ ፓለቲካ በዐማራው ሕዝብ ላይ ያደረሰውን ጥፋት በግልጽ ለማሳየት፣
■ የተፈናቃዮችንና የሟቾችን ማንነት ዝርዝር መረጃ ለማጠናቀር፣
■ በዐማራው ላይ የደረሰውን የጭፍጨፋ መጠን ለማሳየት፣
■ በዐማራው ላይ እየተፈጸመ ያለውን የዘር ማጽዳት ወንጀል ቀጣይነት ያለውና፣ ሆን ተብሎ በዕቅድ እየተፈጸመ መሆኑን ለማሳየት፣
■ ዐማራውና ሌሎች የኢትዮጵያ ነገድ አባላት በወገናቸው ላይ እየተፈጸመ ያለውን ግፍና እልቂት እንዲገነዘቡ ለማድረግ፣
■ ወንጀለኞቹንና ድርጊታቸውን ለማጋለጥና ለሕግ ለማቅረብ፣
የጥናቱ ሥልት፦ ጥናቱ በማኅበራዊ ሳይንስ ጥራታዊ (Qualitiative) አጠናን ሥልት መሠረት የተካሄደ ነው። የጥናቱ ግብዓቶች በጥንቃቄ በተዘጋጁ የተመጠኑ ጥያቄዎች ላይ ተመሥርቶ በተዘጋጁ ቃለመጠይቆች በተሰጡ መልሶች፣ የጥቃቱ ሰለባ ከሆኑ ሰዎች፣ በቃል፣ በጽሑፍ፣ በቦታና በድርጊት የተሰበሰቡ መረጃዎች ናቸው ። ቃለመጠይቆቹ የተካሄዱት በገጽና ድርጊቱ በተፈጸሙባቸው አካባቢዎች ሆኖ፣ የወንጀሉ ሰለባዎች ከሆኑትና ከቤተሰቦቻቸው ጋር ነው። ጥናቱ በተጨማሪም የሰነድ፣ የፎተግራፍና የቦታ ማስረጃዎችን አካቷል። በቃለመጠይቁ የተሳተፉት ሰዎች ምስልና ድምጽም ተቀርጿል። ለዚህ ጥናት 216 ዐማሮች የእማኝ ቃላቸውን በመስጠት በጥናቱ ውስጥ ተሳታፊ ሆነዋል(የየአካባቢው የጥናቱ ተሳታፊዎች ቁጥር ዝርዝር ዝቅ ብሎ በሚገኘው ግራፍ ላይ ተመልክቷል።)
የጥናቱን ተሳታፊዎች ለመምረጥ ስኖው ቦል (Snow Ball) የናሙና አመራረጥ ዘዴ ተግባራዊ ሆኗል። በሁሉም ቦታዎች የተካሄዱት መጠይቆችና ውይይቶች በድብቅ የተከናወኑ ናቸው።
ጥናቱ የተካሄደባቸው አካባቢዎችም፦ ሐረር፣ አርሲ፣ ቤንች ማጂ፣ ጅማ፣ ወለጋ፣ ከማሽ፣ መተከል፣
አፋር(ዐባይ ነጌስ ጎጥ) እንዲሁም ባሕርዳርና ጎንደር ከተሞች ናቸው።
የተለያዩ የጽሑፍና የሰነድ ማስረጃዎች
◾የኢሰመጉ ዘገባዎች ና መግለጫዎች፣
◾የመላው ዐማራ ድርጅት ሊ/መንበር ፕሮፌሰር አስራት የጻፏቸው ደብዳቤዎችና የመኢአድ የተለያዩ ዘገባዎች፣
◾ወንጀሉ በተፈጸሙባቸው አካባቢዎች የነበሩ ነዋሪዎች ለክልልና ለፌደራል መንግሥት በአማርኛና ኦሮምኛ የጻፏቸው ደብዳቤዎች፣
◾አሁን በውጭ አገር በተለይም በአሜሪካ የሚኖሩ በተለይ በሐረር አካባቢ ዐማራውን የፈጁና ያስፈጁ ስም ዝርዝርና እንዲሁም የት እንደሚኖሩና በምን ሥራ ላይ እንደተሰማሩ የሚጠቅስ፣
◾በአገር ውስጥ የሚኖሩ ዋና ዋና ወንጀለኞች ስም ዝርዝርና የተወሰኑቱም አሁን የትና በምን ሥራ ላይ እንደሚገኙ ጥናቱ አጠናቅሯል፣
◾የሟቾች ከፊል ስም ዝርዝርና የተገደሉበት አካባቢ፣ የአገዳደሉ ሁኔታ፣
◾የዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን ዘገባዎች፣ ለምሳሌ የሰብ ሰሃራን ቲቪ ከጉምዝ (12,000 እና ከጉራ ፈርዳ ደግሞ ከ22,000 በላይ ዐማሮች መፈናቀላቸውን የዘገበው)ናቸው።
የፎተግራፍ ማስረጃዎች
◾ባለቤቶቻቸው የተገደሉባቸውና ከዐማራው የተነጠቁ ንብረቶች (ሕንፃዎች)
◾ዘመዶቻቸው ያለቁባቸው እና በዚያም ምክንያት አእምሯቸው የታወኩ ዐማሮች፣
◾ወንጀሉን የፈጸሙ ጥቂት ነፍሰ ገዳዮች፣
◾ወንጀሉን ከፈጸሙት ውስጥ አንድ አእምሮው የታወከ ወንጀለኛ (20 አማሮችን ያረደ)፣
◾የወደሙ ገዳማትና ቤተክርስቲያናት፣
◾በዘር ማጥፋቱ ያለቁ ዐማሮች አፅም
◾ዐማሮች ያለቁባቸው ወንዞችና ገደላገደሉች ፎቶግራፎች (ለምሳሌ 16 ጆንያ ያህል ጭንቅላት የወጣበት ጥርሶ ገደል)
◾ተፈናቃዮች/የዘር ማጽዳት ሰለባዎች፣
◾የተቃጠሉ የዐማራ ቤቶች፣
◾ተፈናቃዮቻቸው ያልተመለሱባቸው ተዘግተው የቀሩ ቤቶች፣
◾የጥቂት ሟቾች ፎቶግራፎች እና ሌሎችም፣ በማስረጃነት በዚህ ጥናት ውስጥ በአባሪነት ተያይዘዋል።
የጥናቱ ግኝቶች
ይህ ጥናት ኢትዮጵያ ውስጥ ከቶ ሊፈጸሙ ይችላሉ ተብለው የማይታመኑ ኢ-ሰብአዊ ድርጊቶችን በስፋት አካቷል። በዐማራው ላይ የተሠራውን ግፍና እልቂት በትክክል በአኃዝ ለማስረገጥ አዳጋች ነው። ይሁን እንጂ ቁጥሩ እጅግ ከፍተኛ እንደሆነ የተሰባሰቡት ማስረጃዎች ያመላክታሉ። በእነዚህ ቤተሰቦቻቸውን ለማስተዳደር አፈር ገፍተው በኖሩና ሠርተው ለመኖር ብቻ ዓላማቸው ባደረጉ የዐማራ ገበሬዎች፣ ነጋዴዎች፣ ወጣቶች፣ ሴቶች፣ ሕፃናትና አረጋውያን ላይ የወረደው የጥፋት በትር አንዴ በሁሉም አካባቢ በተመሳሳይ ወቅት የተካሄደ ሲሆን፣ ሌላ ጊዜ ደግሞ አንድ ቦታ ላይ ብቻ ችግሩ ደርሶ ተሸፍኖ እየቀረና እያሰለሰ የተካሄደ በሰብአውያን ላይ የተፈጸመ ወንጀል ነው።
ሐረርጌ
በብዛቱም ሆነ በወንጀል አፈጻጸሙ አሰቃቂነት ከፍተኛ የዐማራ እልቂት የተካሄደው በሐረርጌ እንደሆነ ጥናቱ ያሳይል። በምዕራብ ሐረርጌ ብቻ (በገለምሶ፣ አንጫር፣ ዳሮ ለቡ፣ ወፊ፣ ዳንሴ ወዘተ) በመሳሰሉ ቦታዎች ከ10,000-15,000 ዐማሮች አልቀዋል።
አሰቦት ገዳም በ 1983 ዓም ክረምት ላይ 16 መነኮሳትና አርድእት እጅና እግራቸው ታስሮ ወደ ገደል ተጥለዋል። በድሬ ደዋ ከተማ ከ 1984 ዓም ጀምሮ በተለያዩ ጊዚያት የመአድሕ አባላት ናቸው በሚል ምክንያት በርካታ ዐማሮች ተገድለዋል።
ወንጀሉ የተፈፀመበት ሁኔታ
የዘር ማጥፋቱ ወንጀል የተፈጸመው በተናጥልና በጅምላ ነው (ለምሳሌ ገለምሶ ውስጥ 21 ሰዎች አንድ ላይ ተገድለዋል)። ሐረር ጋራ ሙለታ «ጅሌቻ» በተሰኘ ገደላማ ቦታ 32 ዐማሮችን የፍጥኝ በሰንሰለት በማሰርና ዓይናቸውን በመሸፈን በጥይት ረሽነዋቸዋል። ከሞቱት ውስጥ ልጅና አባት እንዲሁም ወንድማማቾች ይገኙባቸዋል። 40 ዐማሮች በገጀራ ታርደው ተጥለዋል።
ወንጀሉ የተፈጸመበት መንገድ
በሕይዎት ወደ ገደል በመጨመር፣ (ለምሳሌ በደኖ መግቢያ ካለ «እንቁፍቱ » ገደል ውስጥ። እጅግ ብዙ ዐማሮች በዚህ ገደል የተጣሉ ሲሆን፣ አካባቢው በጣም ከመሽተቱ የተነሳ ኬሚካል በመርጨት ለአንድ ሳምንት እሬሣ ሲለቀም ቆይቷል። እዚህ ገደል ውስጥ የተጣሉት በአካባቢው የሚኖሩ ዐማሮች ብቻ ሳይሆኑ፣ ቁልቢ ገብርኤልን ሊያነግሱ ከተለያዬ የአገሪቱ ክፍሎች የመጡ ክርስቲያኖችም የጥቃቱ ሰለባዎች ሆነዋል።
በተለያዩ ቦታዎች በተለይም፣ በምዕራብ ሐረርጌ-ገለምሶ ወረዳ፣ የዐማራው ነገድ አባላት የተገደሉት እጅግ ዘግናኝ በሆነ መንገድ ነው። ቀስበቀስ አካላቸውን በመቆራረጥና እንዲበሉትም በማስገደድ ነበር። በአካባቢው ያሉት ዐማሮች በብዛት ከመጨፍጨፋቸው የተነሳ፣ ዕድሜያቸው ከ 25 ዓመት በላይ የሆናቸው ሰዎች ብዙዎቹ አባት፣ አጎትና ታላቅ ወንድም የላቸውም። በጊዜው በነበረው የዐማራ የጅምላ ጥፋት ተገድለዋል።
ብልትንና የተለያየ የሰውነት ገላን መቆራረጥን በተመለከተ፣ ለምሳሌ ጋራ ሙለታ ትኖር የነበረች በንግድ ተዳዳሪ ሴት የተገደለችው በዚህ ሁኔታ ነበር። ይህች እታፈራሁ ደጀኔ የምትባል በእህል ንግድ የምትተዳደር ዐማራ በገዳዮቿ እጅ ትገባለች። መጀመሪያም ቢሆን የገዳዮቿን ትኩረት የሳበችው በነበራት ሀብትና ንብረት እንደነበር የጥናቱ ተሳታፊዎች ይናገራሉ።
ገዳዮቿ እታፈራሁን ይዘው አስረው ልብሷን አስወልቀው አካላቶቿን አንድ በአንድ ቆራረጧት። ጡቷን ቆርጠው እንድትበላው ሰጧት። ከመቀመጫዋም ላይ ሥጋ ቆርጠው እንዲሁ እንድትበላው አደረጓት። ብልቷንም እንዲሁ ቆራረጡት። በሰው ልጅ የመጨረሻ የሚባለውን ሥቃይ አሰቃይተው ቆራርጠው ገደሏት። ጥይት ላለማባከን በሚል በሜንጫ አንገት አንገታቸውን በመበጠስ ወደ ገደል ጥለዋቸዋል። በአንካሴ ተወግተው የተገደሉም ነበሩ።
በሳንጃ ገላቸውን በመተልተል(ለምሳሌ ወ/ሮ አልማዝ የሚባሉ አንድ መልከ መልካም ሴት ወደ ሚጣሉበት ገደል ሲወስዷቸው ሰውነታቸው ከብዷቸው ዳገት መውጣት ስላልቻሉ በሳንጃ አንጀታቸውን በመዘርገፍ እያጣጣሩ ገደል ጨምረዋቸዋል)። በሳንጃ ጡት መቁረጥ ሌላው የግድያው መንገድ ሲሆን፣ በደጉ መድኃኒያለም ፈዲስና ቡርቃ 14 ጡታቸው የተቆረጠባቸውን ሴቶች ለማነጋገር ተሞክሮ በሕይወት ሳይገኙ ቀርተዋል። ብዙ ዐማሮች በቢላዋ ታርደው ሞተዋል። ችግሩን ለማዕከላዊ መንግሥት ለማሳወቅ ከአቦምሳ ወደ ናዝሬት ሲመጡ በተለያየ ጊዜ አቤት ባዮችን ከመኪና በማስወረድ 100 ያህል ሰዎችን ገድለዋል።
◾እዚያው ሐረር አካባቢ የሁለት ዐማሮች አገዳደል ለየት ያለነበር። እግርና እጃቸውን ካሰሯቸው በኋላ ልብሳቸውን በማውለቅና ብለታቸውን በመቁረጥ፣ በጥርሳቸው ሲያስነክሷቸው እየፎከሩና እየተሳደቡ ሕይዎታቸው ማለፉን የዐይን እማኖቹ አስረድተዋል።
◾ስሟ በትክክል ለመወቅ ያልተቻለ አንዲት ዐማራ በጅምላ ከተደፈረች በኋላ ጫካ ውስጥ በመውሰድ እጅና እግሯን በምስማር እንጨት ላይ መስቀለኛ መተው ገድለዋት ተገኝታለች፤
◾አንድ ገለምሶ ውስጥ ታዋቂ የነበረች ባለሀብት ዐማራ፣ በጣም የምትወደው አንድ ልጅ ነበራት። ልጇን አርደው የነበራትም የጭነት መኪና ወርሰዋታል። ሴትዮዋ አሁን ኅሊናዋን ስታ የሥቃይ ኑሮ በመግፋት ላይ ትገኛለች። ውሎዋም አዳሯም ጎዳና ላይ ነው።
◾በአሰቦት ገዳም ኩርባ ጀርቲ ገደል የገቡ መነኮሳትና የቤተክርስቲያን አገልጋዮች አገዳደል እጅግ ዘግናኝ ነበር። ዓይናቸውን ካሰሯቸው በኋላ ከጀርባቸው የእሩምታ ተኩስ በመክፈት ከፊታቸው ገደል መኖሩን ያላወቁ እነዚህ ንፁሐን እየሮጡ ወደ ገደል እንዲወድቁ ተደርጓል። አስከሬናቸው መሬት ሳይነካ በየዛፉና ገደሉ ተንጠልጥልጥሎ ለቀናት ይታይ እንደነበር ታውቋል።
◾ሰው ገድላችኋል በማለት በሀሰት ሰዎችን ወደ እስር ቤት በመወርወርና ንብረት መንጠቅም በስፋት ተካሂዷል። (ለምሳሌ የሐረሩ ባለሀብት ለዚህ አንዱ ምሳሌ ናቸው)። በሐረርጌ በዐማራው ነገድ ላይ ያነጣጠረው የዘር ጥፋት ካባባሱት ምክንያቶች አንዱና ዋናው፣ የወቅቱ ጠቅላይ ሚኒስቴር ታምራት ላይኔ በየካቲት 1985 ዓም በድሬደዋ ቁጥር 1 መንገድ አካባቢ በሚገኘው የጫት ላኪዎች ማኅበር አዳርሽና በሚያዚያ ወር በጅጅጋ አደባባይ ያደረገው ጠብ ቀስቃሽ ንግግር ነው። ድሬደዋ ላይ የሰበሰባቸውን ሶማሌዎችን(ኢሳዎች)፣አፋሮችን፣ ከሁለቱም ድብልቅ የሆኑትን ጎርጎራዎችን እንዲሁም ኦሮሞዎችን ሲሆን «ግመል ጎታችና ሽርጣም ሲልህ የነበረውን ነፍጠኛ ለምን ዝም ትለዋለህ!» በማለቱ ችግር ፈጣሪዎችን የልብ ልብ ሰጧቸዋል።
◾በአማራው ላይ በወቅቱ የተፈጸመውን ግፍ/ወንጀል የተቃወሙ የተወሰኑ የኦሮሞ ተወላጆችም ሕይዎታቸውን አጥተዋል። አብዲሽ ሙሜ ይባል የነበረና ወተር ላንጌ በሚባል ሥፍራ ነዋሪ የሆነው ይህ ሰው፣ የራሱ መኪና የነበረውና በትራንስፓርት ዘርፍ የተሰማራ ነበር። ይህንን የወንጀል ድርጊት ይቃወም ስለነበር «ዐማራዎችን በመኪናህ እንዲያመልጡ ረድተሃል» በሚል ሰበብ ከዐማራዎች ጋር ተገድሏል። ሌላው ኦሮሞ ከማል ገና ሲሆን የእስልምና እምነት ተከታይ ሲሆን፣ እየደረሰ የነበረውን ግፍ በጽኑ ይቃወም ነበር። «ለዐማራ ሕዝብ መረጃ አቀብለሃል» ተብሎ በሠራዊት አዛዥ ጥቅምት 17 ቀን 1984 ዓም ወሬንሶ ቀበሌ ላይ ተገድሏል።
አርሲ
የጥናት ውጤቱ እንዳረጋገጠው፣ ኦነግና ኦህዴድ ሕዝቡን በመቀስቀስ በዐማራው ላይ ግድያ እንዲፈጸም፣ ንብረት እንዲዘረፍ አነሳስተዋል። አሰቃቂ እልቂት ፈጽመዋል።
በምዕራብ አርሲ በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ዐማሮች በአሰቃቂ ሁኔታ ሕይዎታቸውን አጥተዋል፤ በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ቤቶች በእሳት እንዲወድሙ ሆኗል፣ (በጀጁ ወረዳ ብቻ 6000 ቤቶች ጋይተዋል፤ ከፍተኛ ንብረት ተዘርፏል። በአሰንሳቦ ወሻቦ በተባለ ቀበሌ ብቻ 1115 የቀንድ ከብቶች ተዘርፈዋል ።
በአርባጉጉ አውራጃ በነበሩ 6 ወረዳዎች ውስጥ ይኖር የነበረው ዐማራ እጅግ ብዙ ነበር። ከእርስ በርሱ እልቂት በኋላ ብዙዎቹ ሲሞቱ፣ በሕይዎት የተረፉት ወደ ተለያዩ ያገሪቱ አካባቢዎች ተበትነዋል። በአርባ ጉጉ፣ በጉና ወረዳ ሞሶ ጊዎርጊስ ገደል ብቻ ከ 500 ያላነሱ ሰዎች በሕይዎት ወደ ገደል ተጥለዋል።
በጥቅሉ በዐማራው ላይ ከታች የተዘረዘሩት ችግሮች ደርሰውበታል፦
◾ሀገር ማስለቀቅ(ማፈናቀል፣)
◾ሰዎችን ማረድ/ መግደል፣
◾ሃይማኖትን ማጥፋት(ማስቀየር)፣
◾ትጥቅ ማስፈታት፣
◾ንብረት መዝረፍና ቤት ማቃጠል፣
◾ልጃ ገረዶችን መድፈር ፤ አስገድዶ ማስለምና ማግባት፣
በምዕራብ አርሲ ከ1983 ጀምሮ ሁለት ጊዜ ከፍተኛ እልቂት በዐማራው ላይ ተፈጽሟል። የመጀመሪያው በ1983/4 ዓም ሲሆን፣ ሁለተኛው ደግሞ በ 1998 ዓም ነው። በችግሩ ውስጥ ያለፉትን ዐማሮች ለማነጋገር ተሞክሮ በፍርሃት ለመተባበር ፈቃደኛ ሳይሆኑ ቀርተዋል። በኢሰመጉ ዘገባ መሠረት ከፍተኛ እልቆት በዐማራው ላይ መፈጸሙ ተረጋግጧል።
ጂማ
በ1999 ዓም የጥቅምት አቦን ለማክበር በበሻሻ በተሰባሰቡ አማሮች ላይ የደረሰው ዘግናኝና ሰቆቃ ለመተረክ እጅግ ያዳግታል። ሕፃናት፣ ሴት፣ ወንድ አዛውንት፣ ቄስ ወዘተ ሳይል፣ ሁሉም ድንገት ወደ ንጋቱ ላይ በተከበቡ ሰዎች ገጀራ እንደ እንሰሳ ገላቸው እየተቆራረጠና እየተጎመደ ነበር የወደቀው። ብዙ ሰዎች አለቁ። ሁኔታውን የሚቆጣጠር ምንም ኃይል አልነበረም።
በጂማ ዞን ሸቤ ወረዳ ውስጥ 400 የሚሆኑ አባወራዎች ከ 2000 በላይ ቤተሰቦቻቸው ጋር ተፈናቅለዋል። የሸቤ ወረዳ ከጂማ ከተማ ወደ ቦንጋና ሚዛን በሚወስደው መንገድ 83 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ትገኛለች። ይህች ከተማ ለወሬ ነጋሪ የቀረ አማራ የለባትም። ሁሉም ቤታቸው ተቃጥሎ «ደን አውዳሚ» ተብለው ንብረታቸው ወድሞ ተሸኝተዋል። በ 2004 እና 2005 የተፈናቀሉ ዐማሮች ቁጥር ከ20,000 በላይ እንደሆነ እማማኞች ይስማማሉ።
ጉራፈርዳ
ጉራፈርዳ በደቡብ ክልል በቤንች ማጂ ዞን የሚገኝ ወረዳ ነው። ይህ ክልል የዐማራውን የዘር ማጥፋትና የዘር ማጽዳት ወንጀል በስፋት የተፈጸመና የዐማሮች ደም በእጁ ያለ አንዱ ክልል ነው።
◾በጉራ ፈርዳ በ 2007 ያውም በወረዳው የሴቶች፣ ሕፃናትና ወጣቶች ጉዳይ ጽ/ቤት በተዘጋጀው ሪፓርት መሠረት እንኳ ከ 3364 በላይ ሕፃናት፣ እናቶችና ነፍሰ ጡር ሴቶች በአንድ ወር ውስጥ ተፈናቅለዋል። 860 ከ 5 ዓመት በታች የሆኑ ሕፃናት ጎዳና ላይ ተበትነዋል።
◾በቅርቡ በ2004 እና 2005 ዓም የተፈናቀሉ ዐማሮች ቁጥራቸው ከ 20,000 ይበልጣል። የሳብ ሰሃራን ቴሌቪዢን ቁጥሩ ከ 22,000 በላይ እንደሆነ ዘግቧል።
◾በ 2007 ዓም በዚሁ ወረዳ ሌላ የተቀነባበረ ግድያና መፈናቀል ተፈጽሟል። ለዚህ ዝግጅት እንዲያመቻቸው መጀመሪያ የጉራ ፈርዳ አስተዳደር የዐማሮችን መሣሪያ እንዲወርስ አደረጉ። ያን ከዐማራው የነጠቁትን መሳሪያ ለመዠንገር፣ ሜንኢትና ሸኮ ነገዶች አስታጠቋቸው። በዚያን ወቅት በተካሄደ ጥቃት በ ትንሹ 600 ሰዎች ተገድለዋል። በመዠንገር፣ ሜንኢትና ሸኮ ነገዶች ገጀራ መያዝ የተለመደ ነው። ዐማሮች ገጀራ መያዝ አይፈቀድላቸውም። ገጀራ ይዘው ከተገኙ ይቀማሉ። መቀማታቸው ብቻ ሳይሆን፣ የአንድ ገጀራ ዋጋ በአማካይ 150 ብር የገዙትን ገጀራ፣ ከቀሙ በኋላ 100 ብር ከፍለው እንዲወስዱ ይደረጋል። የዐማሮችን ንብረት በመቀማትና ብር እየተቀበሉ መመለስ እንደ ገቢ ምንጭ አድርገው የሚኖሩ የአካባቢ ባለሥልጣናት በብዛት አሉ። ዐማራው እስከዚህ የዘቀጠ ደረጃ መብቱና ስብእናው ተደፍሮ ኢትዮጵያ በሚላት አገሩ በሁለተኛ ዜግነት ይኖራል።
ወለጋ
ወለጋ ውስጥ በዐማራው ላይ የተፈጸመው ሰቆቃ ከላይ ከተጠቀሱት አካባቢዎች ይበልጥ እንጂ አያንስም።
◾ወለጋ ውስጥ በአንቀልባ ይታዘሉ የነበሩ 40 ሕፃናት በጥይትና በእሳት ተቃጥለው አልቀዋል። በጊዳ-ኪራሞ ወረዳ የኦሮሚያ ልዩ ኃይል፣ ፈጥኖ ደራሽ ፓሊስና የመከላከያ ሠራዊት በጋራ በዐማሮች ላይ በከፈቱት መጠነ ሠፊ ጦርነት ከ 1110 በላይ ዐማሮች ተጨፍጭፈዋል። በጠቅላላ ከ25,000 በላይ ዐማሮች ከወለጋ ተፈናቅለዋል።
◾እዚያው ወለጋ ውስጥ በአቢደንጎሮ የዐማራ ባለትዳር ሴቶች በኦሮሞዎች የተወሰዱ ሲሆን፣ አራት እማወራዎች ተደፍረዋል። የዐማሮች ሀብትና ቤት ለኦሮሞዎች ተከፋፍሏል። ማን የማንን ቤት እንደሚዘርፍ፣ ማን የማንን ሚስት እንደሚቀማ እቅድ ከመውጣቱም በላይ «ወሎ ወሎ ነው ዝም ብለህ በለው! ዐማራ ዐማራ ነው ዝም ብለህ በለው!» በማለት በዐማሮች ላይ የጥይት እሩምታ ተከፍቶ በጅምላ እንዲያልቁ ተደርጓል። አንዳንዶች በቤታቸው እየተዘጋባቸው ተቃጥለዋል። ጋሬሮ ላይ አንዲት ወልዳ የተኛች ሳምንት ያልሞላት ደካማ እመጫት ዐማራ አዲስ ከተወለደው ሕፃን ጋር በቤቷ ውስጥ ተቃጥላለች። ሰኔ ወር 1992 ዓም በተጠቀሱት ወራዳዎች«ዐማራ ወደ አገርህ ግባ» የሚሉ ማስታወቂያዎች በወረዳው ባለሥልጣናት ይለፈፉ ነበር። በርካታ ሰዎች ተደበብድበዋል።የጋሬሮ ማርያም ቤተክርስቲያን ተቃጥላለች። ነዋየ ቅዱሳቷ ተዘረፈዋል። የዐማራ ከብቶች ተዘርፈው ተነድተዋል። ሌላም ሌላም ግፍ ተፈጽሟል። አገዳደሉም በጥይት በመደብደብና ከባድ መሣሪያ በመጠቀምም ነበር፤ ለምሳሌ የፓሊስና መከላከያ ሠራዊት ያደረጉት ይህንን ነው። በመኖሪያ ቤታቸው ውስጥ እያሉም በእሳት በማቃጠል ፈጅተዋቸዋል። አንዲት የ 45 ዓመት ነፍሰ ጡር በጥይት ተደብድባ ተገላለች።
አፋር
ሁሉም ዐማራን ጨምሮ ዐማራውን ለማጥፋት ያልተነሳ ጎሳ እንደሌለ ግልጽ ሆኗል። በአፋር የሆነውም ከፍተኛ ሰቆቃ ማመን የሚያዳግት ነው። ዐባይ ነጊሶ ቀበሌ የዐማራ ክልል ሆኖ ከቆየ በኋላ ሀሳቡ ከየት እንዳልመጣ ባልታወቀ መንገድ እና ግማሹ ዐማራ ደግፎታል ተብሎ ወደ አፋር ክልል እንዲቀላቀል ተደረገ። የቀበሌው ነዋሪዎች በሙሉ ዐማሮች ሆነው ሳለ፣ ለምን ወደ አፋር ክልል ተመደቡ? ቀበሌው ወደ አፋር እንደተካለለ የዐማሮቹ ይዞታ ለኢንቬስተር ተሰጠ። ኢንቬስተሩ በአካባቢው ያጋጠመውን ችግር መቋቋም ተስኖት ወዲያው ለቆ ወጣ። መሬታቸውን የተነጠቁት ዐማሮች ለኢንቬስተሩ የቀን ሠራተኛ በመሆን ኑሯቸውን ለመግፋት ሞክረዋል። ከዐማሮቹ ተነጥቆ ለኢንቬስተሩ ተሰጥቶ የነበረው መሬት እንደገና ለ44 አፋር ለ 16 ዐማራ ተከፋፈለ። ከ2000 ዓም ጀምሮ አፋሮች ከዐማሮች ላይ እንደገና የቀረውን መሬት እየነጠቁ ለሚፈልጉት ሰው መስጠት ጀመሩ። ዐማሮች «ለምን?» ብለው ሲጠይቁ «አገሩ እኮ የእኛ ነው» የሚል መልስ ተሰጣቸው። አንዱ አስገራሚው ታሪክ የ ወ/ሮ በርዬ ነጋሽ 50 ሜትር በ 50 ሜትር የሆነ ባቡር በሚሠራው የቱርክ ኩባንያ ተወስዶ ለነበረው መሬታቸው 246,000 ብር ካሳ ሲመደብላቸው፣ የወረዳው ፓሊስ አዛዥ ሻለቃ አብዱ አህመድ ለራሱ ወስዶታል።
መጨረሻም ችግሩ ተባብሶ ለዐማሮች ሕይዎት መጥፋት ምክንያት ሆነ። በዐባይ ነጌሶ ጎጥ ይኖሩ የነበሩ ዐማሮች እየተገደሉ፤ እየተሰደዱና እየተፈናቀሉ ቁጥራቸው ቀንሷል። በአካባቢው በአሁኑ ወቅት ከ 250 በታች አባወራ ዐማሮች ብቻ ይኖራሉ። 52 ሰዎች በአፋሮች ተገድለዋል። 96 ሰዎች በቀይ ባሕር አድርገው ወደ ሳውዲ ዓረቢያና ሌሎች አገሮች ተሰደዋል። እዚህም ዐማሮች ማናቸውም የራስ መጠበቂያ ይነጠቃሉ፣ ባዶ እጃቸውን ሲሆኑ አፋሮቹ ይጨርሷቸዋል። በዓመት በአማካይ በዚህ ቀበሌ ብቻ 20 ዐማሮች ይገደላሉ። ዐማሮች መድረሻ አጥተዋል። በየዕለቱ ከሞት ጋር ግብ ግብ እንደገጠሙ ይኖራሉ።
ዐማራ ክልል
ሌላው የወንጀሉን አስከፊነት የሚያሳየው የዐማራ ክልል በተባለው ስፍራ የተካሄደው የዘር ማጥፋት ወንጀል ነው። አብላጫ ነዋሪ ዐማራ በሆነበት መተከል ዞን ውስጥ ከ 10,000 በላይ ዐማሮች ሞተዋል። በጊዜው የነበረ ቡለን ተወልዶ ያደገ ጎልማሳ ስለሁኔታው እንዲህ ይላል።
«በአብዛኛው የመተከል ጫካዎች ያለቀው ዐማራ ቁጥር እጅግ ብዙ ነው። በትኑሹ ከ አስር ሺህ በላይ ሕዝብ አልቋል። ያለ ምንም ማጋነን ከ50 እስከ 100 ሜትር ባለ ርቀት መካከል የአንድ ወይም የብዙ ሰዎችን አስከሬን ወዳድቆ ማየት ብዙም የሚገርም አልነበረም። ከሙታኑ የሚመጣው ሽታም መጥፎ ጠረን ፈጥሮ ነበር። አሁን በሥልጣን ላይ ያሉ ሰዎች በጊዜው ችግሩን እንዳባባሱት አምናለሁ። ደመቀ መኮንን (የአሁኑ ምክትል ጠ/ሚኒስትር )መንታ ውሃ አካባቢ ሰዎችን አደራጅቶ የጦርነቱ ዋነኛ ተዋናኝ እንደነበረ ሁሉም ሰው ያውቃል።»
◾በዐማራ ክልል አዊ ዞን ጃዋ አካባቢ የሠፈሩት ዐማሮች የሠፈሩበት ቦታ ባለመመቸቱ ብዙዎቹ በበሽታ አልቀዋል። የወባ ወረርሽኚን ለመከላከል የሚያስችል ሥራ ባለመሠራቱ አንድ ዓመት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ 1,000 የሚሆኑ ዐማሮች በወባ አልቀዋል። ከሰዎቹ እልቂት በተጨማሪም 7,000 የሚሆኑ የቀንድ ከብቶች በገንዲ በሽታ አልቀዋል። ይህ ሁሉ ሲሆን የክልሉም ሆነ የፌደራል መንግሥት ሊደርስላቸው አልቻለም።
◾በመተከል የተካሄደውም ጭፍጨፋ ከሐረሩ እንደማይተናነስ የጥናቱ ተሳታፊዎች ያምናሉ። ከሞቱት ሌላ 60,000 ያህል ዐማሮች ከተወለዱበትና ካደጉበት ቦታ ተፈናቅለዋል። በመተከል የተካሄደው ጭፍጨፋ የመጀመሪያው ወያኔ ሲገባ በ 1983 ዓም የሆነው ሲሆን፣ ሁለተኛውና አስከፊው ደግሞ ከ 2004ዓም ጀምሮ የሆነው ነው።
◾በርካታ ሰዎች ከነሕይዎታቸው በቤታቸው ውስጥ ተቃጥለዋል። ብዙዎች ተገድለው ብልታቸው በስለት የጀብድነት ምልክት ተደረጓል። ሴት፣ ወንድ፣ ሕፃንና ሽማግሌ ሳይለዩ 270 ሰዎች በጥይት ተደብድበው ተገድለዋል። በ 9 ቀበሌ ገበሬ ማኅበራት ውስጥ 6833 ቤቶች ተቃጥለው ነዋሪዎቹ ተፈናቅለዋል። ከ 60,000 ሰዎች በላይ ከአደጉበትና ከኖሩበት ቀዬ ከጥቃቱ ፍራቻ የተነሳ አካባቢውን ለቀው ወጥተዋል።
◾ሁለት የወረዳ አስተዳዳሪዎች ሰኔ 12 ቀን 2004 ዓም ዐማራውን ሰብስበው «የዐማራ ተወላጅ የሆናችሁ የማዳበሪያና የማይክሮ ፋይናንስ ብድር ያለባችሁ እየከፈላችሁ ለቃችሁ ውጡ» ብለው ቀጭን ትእዛዝ አስተላለፉ። አቤት የሚባልበት የለ። ዕርዳታ የሚያደርግ መንግሥት በሌለበትና ጎጠኞች በሚፈንጩባት የዛሬዋ ኢትዮጵያ ዐማሮቹ ግራ ቢጋቡ «እስከ ጥር 30 ቀን 2005 ዓም ሰብል ሰብስበን እንድንወጣ ታገሱን» አሉ። «ጥር 30 ቀን 2005 ዓም ልትወጡ ፈርሙ!» ምን ምርጫ አለ!ሁሉም ፈረሙ!በመተከል ዞን በሁሉም ወረዳዎች የዘር ማጽዳት /ማፈናቀል ወንጀል ተካሂዷል። የተካሄደው ኢ-ሰብአዊ ድርጊት እጅግ ብዙና ከፍተኛ መረጃዎችም የተጠናቀሩበት አካባቢ ነው።
ቤን ሻንጉል ጉምዝ
በ 2007 ዓም የተከናወነውን ምርጫ ምክንያት በማድረግ በርካታ የቤንሻንጉል ጉምዝ ክልል ልዩ ኃይል ፓሊሶች ወደ መተከል ዞን ተመደቡ። ቡለንና ወንበራ ወረዳዎች ውስጥ የተመደቡት ፓሊሶች ዐማሮችን እየሰበሰቡ በጣቢያ ያስሯቸው ጀመር። ለዚህም የተሰጠው ምክንያት «ዐማራ ብዙ የጦር መሣሪያ ስላለው ምርጫውን ያውካል» የሚል ነበር። መሳሪያ ሳይኖራቸው መሳሪያችሁን አውጡ በሚል በርካታ ሰዎች ተደበደቡ። በመተከል ዞን ያሉ ባለሥልጣናት «ዐማራን ብናፈናቅለው ክልሉን እያሳጣ ስም ያጠፋል። እናንም ያስጠይቃል። ስለሆነም ባሉበት መጨረስ ይሻላል» የሚል ቅስቀሳ ጀመሩ።
በማን እንደተገደለ ሳይታወቅ አንድ ጉምዝ ወንበራ ወረዳ ሞቶ ተገኘ። አካባቢው በወንበራ ወረዳ ሆኖ ወደ ቡለን ወረዳ አጎራባች ቀበሌ ነው። ሆን ተብሎ፣ የታቀደበት በሚመስል መልኩ የሁለቱ ወረዳዎች አጎራባች ቀበሌዎች ሁሉንም ጎሳ እየለዩ በአንድ ቀን ሰበሰቡ። ዐማሮች ላይ ሲደርሱ «የገደለውን አውጡ!» አሏቸው። ሆኖም ሁሉም ዐማሮች የተገደለበትን ምክንያትና ማን እንደገደለው እንደማያውቁ ተናገሩ። ከሁለቱም ወረዳዎች የመጡት ባለሥልጣናት ቀበሌ ላሉት የጉምዝ ጎሳ አባላት «የገደለውን እንዲናገሩ አድርጓቸው» ብለው መድረኩን አስረክበው ሄዱ።
ከዚያ በኋላ ደም እንደውሃ ፈሰሰ። ግንቦት 7 ቀን 2007 ዓም በወንበራ ወረዳ በተለይም በመልካን ቀበሌ ሞት ነግሦ ዋለ። እስከ 160 የሚደርሱ ሰዎች በቢላዋና በገጀራ ታረዱ። ሮጠው ለማምለጥ የሞከሩ ጥይት ቀደማቸው። በቤታቸው የነበሩ ቤተሰቦች ለወሬ ነጋሪም ሳይተርፉ ሁሉም ታረዱ። የሚተኙበት አልጋ በደም ራሰ። ነፍሰ ጡር እናቶች ለመውለጃ ጊዜ አላገኙም። 9 ወር የሆናቸው ጽንሶች ተጨናገፉ። በሆድ ውስጥ ያሉት ጽንሶች በጉምዝ ቢለዋ ተቀደው ወጡ። የሙታን እጆችና መዳፎች እየተቆረጡ ለከበሮ መምቻ ሆኑ። ሌላም ሌላም ለጆሮ የሚሰቀጥጥና ለሰሚው ግራ የሚሆኑ ድርጊቶች ተፈጸሙ። በቤን ሻንጉል ጉምዝ ክልል በተለያዩ ዞንና ወረዳዎች ውስጥ ይኖሩ የነበሩ ከ 10,000 በላይ ዐማሮች ተገድለዋል። ከ 10,000 በላይ ዐማሮች ለረዥም አመታት ከኖሩበት ቦታ ተፈናቅለዋል።
ምዕራብ ሸዋ
በምዕራብ ሸዋ ዞን ኖኖ ወረዳ የኦሮሚያ ባለሥልጣን ተብዬዎች ሕዝብን በሕዝብ ላይ አነሳስተዋል። ለሕይዎትም መጥፋት ቀጥተኛ ምክንያት ሆነዋል። በተለይ መጋቢት 27 ቀን 2007 ዓም አቶ ዘውዱ እንዳለ የተባለ የኦሮሞ ነገድ ተወላጅ ተገድሎ ይገኛል። «ይህ ግድያ የተፈጸመው በዐማራ ብሄረሰብ ተወላጆች ነው» በማለት የኖኖ ወረዳ ፓሊስ አዛዥ ኢንፔክተር ኃይሉ ዲሪባ፣ የኖኖ አሎ ቀበሌ ሊ/መንበር አቶ ጎሣዬ ገችና መቶ አለቃ ገነነ በየነ የተባሉ የፓሊስ አባላት የቀበሌና የፓሊስ አባላትን በማስተባበር የአካባቢው ሕዝብ በአካባቢው በሚኖሩ የዐማራ ነገድ ተወላጆች ላይ እንዲነሳሳ በማድረግ ሚያዚያ 9 ቀን 2007 ዓም 85 አርሶ አደር አባወራዎችን ለእስር ከዳረጓቸው በኋላ ቅዳሜ ማለትም ሚያዚያ 10 ቀን 2007 ዓም ከጠዋቱ 3 ሰዓት አካባቢ ዘር በመምረጥ የዐማራ ተወላጆች መኖሪያ ቤትና ንብረት ነው ያሉትን እየመረጡ በእሳት እንዲቃጠሉ አደረጉ። የታሰሩትን አባወራዎችንም ለነዳጅ በማለት ከእያንዳንዳቸው 300 ብር ከተቀበሏቸው በኋላ ቤታችሁ ተቃጥሏል ሂዱ በማለት ከእስር እንደለቀቋቸው ለኢሰመጉ በቀረበ ማመልከቻ ለማረጋገጥ ተችሏል። የኢሰመጉ ባለሙያዎችም በቦታው ተገኝተው ሁኔታው አጣርተው ዕውነትነቱን አረጋግጠው ስለሁኔታው በተለመደው ሪፖርታቸው ለሚመለከተው አሳውቀዋል። በዚህም በርካታ ሰዎች ተገድለዋል። በበርካታ ሰዎች ላይ የመቁሰልና የአካል ጉዳት ደርሷል። ብዙ ቤቶች በእሳት ጋይተዋል።
ዐማራውን ለማስጨፍጨፍ የተካሄዱ የፈጠራ ቅስቀሳዎች፤
የትግሬ-ወያኔ መንግሥት እና የእርሱ ግብረ አበር የሆኑት ኦሕዴድ እና ኦነግ የተለያዩ የሀሰት የቅስቀሳ መንገዶችን በመጠቀም ባሰራጩት ቅስቀሳ፣ ዐማራው ላይ ለደረሰው የሕይዎት ጥፋት፣ የሀብት ነጠቃና፣ ከአካባቢ የመፈናቀል ድርጊቶች ፈጽመዋል ። ይህንንም ለማድረግ ሆን ብለው የተፈጠሩ የጠብና የማሳበቢያ መንገዶችን በመጠቀም ነው። ይህ ሁኔታ ዐማራው በተፈናቀለባቸው አካባቢዎች ሁሉ ተግባራዊ የሆነ ነው።
◾በተለያየ ምክንያት የሞቱ ሰዎችን፣ ዐማሮች እንደገደሉ በማስመሰል የሀሰት ወሬ በማናፈስ ዐማራውን የጥቃት ሰለባ እንዲሆን ተገርጓል፤ ለምሳሌ የሐረሩ ባለሀብት አቶ ደጀኔ በቀለ፣ በሐረር ከተማ የደሴ ሆቴል ባለቤት ያልፈጸሙትን ወንጀል ፈጽመሃል ተብለው ተሰቃይተዋል። ያላደረጉትን የደረቀ እሬሳ ከመቃብር በማስወጣት የእኒህን ንፁሕ ዜጎች ንብረት ወርሰዋል። ገደሉት የተባለው ሰው አዲስ አበባ በሕይዎት በመገኘቱ ንብረታቸው እንደወደመ ቢቀርም ብዙ ሕዝብ ያወቀው ጉዳይ በመሆኑ ሕይዎታቸው ሊተርፍ ችሏል።
◾በምዕራብ ሸዋ ዞን ኖኖ ወረዳ ውስጥ የአካባቢው የኦሮሞ ባለሥልጣናትና የፀጥታ ኃላፊዎች በአካባቢው ይኖሩ የነበሩትን ዐማሮች «እናንተ የዚህ አካባቢ ተወላጅ ሳትሆኑ ሀብት እያፈራችሁ የአካባቢው ተወላጅ ግን ከእንናተ ያነሰ ገቢ ያላቸው ናቸው። ይህንን ገቢ ያገኛችሁት በእኛ መሬት ላይ ነው፤ ስለዚህ የክልሉ ተወላጅ ባለመሆናችሁ ክልሉን ለቃችሁ ውጡ።» እያሉ ንብረታቸውን በመንጠቅ እነዚህን አርሶ አደሮች በተለያየ ጊዜ ለእስር ዳርገዋቸዋል። ለአካባቢው ሕዝብም «በእናንተ መሬት ነው ሀብት ያፈሩት ….» እያሉ ጥላቻና ግጭትን በሥፋት ሰብከዋል።
◾በ 1992ዓም ምርጫ ወቅት ኮፈሌ አካባቢ «አገርህን የአማራ ሕዝብ አጠፋልህ» የሚሉና ሌሎች የተንኮል ቅስቀሳ ጽሑፎች በገጠር ለሚኖረው ኦሮሞ ተበትኖለት ነበር። በዚያ ዕኩይ ቅስቀሳ ሕዝብን በሕዝብ ላይ በማነሳሳት አያሌ ዐማሮች ባንድ ምሽት በቆንጨራ ተጨፍጭፈው እንዲያልቁ ተደርጓል። ሁኔታው ሲረጋጋ ሕጋዊ እርምጃ ተወሰደ ተባለና ወንጀሉን የፈጸሙት ቀርተው ጭራሹን ተጠቂዎቹ ዐማሮች እንዲሆኑ ተደርጎ በዕድሜ ልክ እሥራት ወህኒ እንዲወርዱ ተደርጓል።
◾በምዕራብ አርሲ ዐማሮችን ለማጥፋት ሲጠነስሱ ከቆዩ በኋላ ዕኩይ ተግባራቸውን ለማስፈጸም የኦሮሞውን ማኅበረሰብ ለማነሳሳት፣ በተለይ በ 97ቱ ምርጫ ወቅት «ቅንጅት የምኒልክ ዘር ነው። አማራ ተመልሶ ሊገዛህ ነው!! የኦሮሞ ሕዝብ ተመልሶ በአማራ የፊውዳል ሥርዓት ሥር መውደቅ የለበትም።» የሚሉ ቅስቀሳዎች ተካሂደዋል። በዚህ ቅስቀሳም ዐማራው በገፍ እንዲገደል ሆኗል።
ከምርጫው በኋላም ዐማራውን ለመጨፍጨፍ ሆን ብለው «የምኒልክ ዘር ተነስ ፤ የሰለሞን አጥንት ይወጋሃል፤ሥልጣንህን ለኦሮሞ አሳልፈህ አትስጥ!ሥልጣን ከመሠረቱ ያማራ ነው!» የሚል በራሪ ወረቀት አዘጋጅተው ገበያ ላይ ረጩ። በዚህና በሌላ ተጨማሪ ቅስቀሳ ሳቢያ በኮፈሌ ከተማ ውስጥ የበርካታ ዐማሮች ደም ፈሰሰ።
◾ጂማ ውስጥ «ደን ጨፍጫፊዎች» ተብለው በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ዐማሮች ተፈናቅለዋል፤ እንዲሁም ተገድለዋል።
◾ምሥራቅ ወለጋ ላይ ከኦሮሚያ የተለያዩ ክልሎች የተውጣጡ ባለሥልጣኖች ዐማሮችን ከኦሮሚያ ሙሉ በሙሉ ለማስወጣት «አማሮች የአገራችንን “አሮሚያን“ ደን አውድመዋል፤ የአማራ ክልል መንግሥት ያለባቸውን የማዳበሪያ እዳ ሳይከፍሉ የመጡ በመሆናቸው ይመለሱልን» የሚሉ ምክኒያቶችን በመደርደር ሁሉም በአካባቢው የሚኖሩ ዐማሮች ከሰኔ 8 እስከ 16 ቀን 1992 ድረስ እንዲወጡ ውሳኔ አስተላልፈዋል።
◾ዐማራ ክልል ውስጥ (ቢሮክራሲና የፊውዳል ቅሪት) ተብለው አርሰው የሚበሉት መሬት ተነፍገዋል።
◾ወለጋ ውስጥ(ዐማራ ወደ አገርህ ግባ) በሚል በኦሆዴድ ባለሥልጣናት ተዘውትሮ ይለፈፉ ነበር።
◾ከዚህም በተጨማሪ የዐማራውን ሥብዕናና ማንነት የሚያንቋሽሹ ጸያፍ አባባሎች በየአካባቢው ይሰነዘሩ ነበር። ከፍ ብሎ የተጠቀሱት ወ/ሮ አልማዝ የአቶ አበበ ምትኬ ባለቤት በሰውነታቸው ክብደት ምክኒያት ወደ ሚጣሉበት ገደል አፋፍ ለመውጣት ሳይቻላቸው ይቀራል ፤ በመሆኑም በሳንጃ ሆዳቸውን ሲዘረግፏቸው «አፋን አጅዋ አማራ!» (ግም አፍ አማራ) በማለት ይሰድቧቸው ነበር።
◾መተከል ውስጥ አንድ የወረዳ አስተዳዳሪ እንዲህ የሚል አጸያፊ ቃል ተናገረ «እናንተ ዐማራዎች በሄዳችሁበት ሁሉ እንደ ቁንጫ እየተራባችሁ ብሄረሰባችንን ልታጠፉት ነው!አባይስ ተገድቦ ቆመ የእናንተ አማራዎች ስደት መቼ ነው የሚቆም!»
◾በቤንች ማጂ ዞን ከጥር ጀምሮ ደን ማቃጠል የተለመደ ባህል ነው። የአካባቢው አርብቶ አደሮች የደረቀውን ሣር አቃጥለው ሌላ አዲስ እንዲበቅልላቸው ስለሚፈልጉ ያቃጥሉታል። ይህንን ታዲያ ዐማሮች እንዳቃጠሉት ተደረገና በዞኑ የሚኖሩ ዐማሮችን ለማፈናቀል ታቅዶ ሶስት «ሕጋዊ ከለላ» የተሰጣቸው መስፍርቶች ወጡ። እነርሱም (1)ሕገ ወጥ ሰፋሪ ማለት፦ ፈቃድ ሳያገኝ ወደ አካባቢው መጥቶ የሚኖር፣ (2) ደን አውዳሚ «ጫካ የሚመነጥርና የሚያቃጥል»፣ (3)ጠብጫሪ ፣«ከነባር ሕዝቦች ጋር በሰላም የማይኖር» የሚሉ ናቸው።
ጥቃቱ በሕይዎትና ባሉት ላይ ያሳደረው የሥነልቦና ችግር፤
በዐማራው ላይ የተሰነዘረው ጥቃት በሕይዎት በተረፉት ላይ ምን ያህል ሽብርና የሥነልቦና ስብራት ውስጥ እንደከተታቸው የሚያሳየው ማስረጃ ከሁሉም ስሜትን የሚፈታተነው ነው።
◾ለምሳሌ ሐረር ፣ ወተር በተባለው ስፍራ ወንድሙና አባቱ የተገደለበት ግለሰብ በአጥኚው ቡድኑ ሁኔታውን እንዲያስረዳው ላቀረበለት ጥያቄ የሰጠው መልስ፣ ከፍራቱ ብዛትና ይከተለኛል ካለው የጥቃት ምንነት ተነስቶ ፍራቱ ያሳደረበት ዕውነታን የመካድ ስሜት ውስጥ ገብቶ፣ «ይህን አንተ የምትለውን ነገር እንኳን ላየው በራዲዮም ሰምቼው አላውቅም» ነው ያለው።
◾እዚያው ሥፍራ አንድ አዛውንት ደግሞ «አይ እኔ አሁንም እኮ ያለሁት ከእነርሱ መካከል ነው! ድምፄንና ምስሌን አትቅዱ!በወረቀት መጻፍ ትችላላችሁ» ነበር ያሉት።
◾ሌላው የ 80 ዓመት አዛውንት በድብደባ ብዛት መንቀሳቀስ የማይችሉና አብረዋቸው የነበሩ ዐማሮች ሁሉ ሲያልቁ እሳቸው በዕድል የተረፉ ናቸው። ድምፃቸው እንዲቀረጽ ለምን እንደማይፈልጉ አጥኚው ቡድን ሲጠይቃቸው «እንደ አበበ ምትኬ መዓት ቢወርድብኝስ» በማለት ፍርሃታቸውን ሳይደብቁ ተናግረዋል። አቶ አበበ ምትኬ የተባሉት ግለሰብ ከወተር አጎራባች በደኖ ከተማ ውስጥ የሚኖሩ ዐማራ ነበሩ። በመጋቢት ወር 1984 ዓም የተካሄደውን የዐማራ እልቂት አስመልክተው ለጋዜጠኞች መረጃ ሰጡ። ይህንን የአካባቢው አስተዳዳሪ ኦነግ ይሰማል። ከዚያም የአቶ አበበ ምትኬን ዘጠኝ የቤተሰብ አባላት ከነነፍሳቸው እንቁፍቱ ገደል ጨምሯቸዋል። አቶ አበበ ምትኬ ይህ ከሆነ ከሁለት አመት በኃላ በንዴትና ብስጭት ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል።
የዚህን ጥናት ዝርዝር ዘገባ ማንበብ እጅግ ስሜትን ይፈታተናል። የሰዎችን ጭካኔ ባንድ በኩል፣ በሌላ በኩል የሟቾችን ሰቆቃና ጣር ላየ በስሜትና ጥላቻ ላይ ድንቁርና ተጨምሮበት አደጋው ምን ያህል አስከፊ እንደሆነ በግልጽ ያሳያል። ይህ አቻ የሌለው ወንጀል መቆም አለበት። ወንጀለኞች ለሕግ መቅረብ አለባቸው። የመንግሥት ኃላፊነት የአገሩን ዜጋ ደህንነትና መብት ማስጠበቅ ነው። ይህን ማድረግ የሚችል መንግሥት ደግሞ የግድ ዲሞክራሲያዊ መሆን አይጠበቅበትም፤ የመንግሥት ባህላዊና ታሪካዊ ከሆኑት ተግባሮች አንዱና መሠረታዊ ነው። በአገራችን በሕዝባችን ጫንቃ ላይ በመሣሪያ ኃይል የተፈናጠጠው ወያኔና ግብረ አበሮቹ ዲሞክራሲያዊና ሰብአዊ ሊሆኑ ቀርቶ የመንግሥትን ሚና የሚያውቁ ባለመሆናቸው በሚገዙት ሕዝብ ላይ የዘር ማጥፋትና የዘር ማጽዳት ወንጀል ሆን ብለው፣ አቅደውና አልመው ይሠራሉ። የወያኔዎች መንግሥት ይህንን የሕዝብን ሰብአዊና ዲሞክራሲያዊ ጥቅሞችና መብቶች ለማስከበር ቀርቶ፣ የመንግሥትነት ባሕሪ የለውም። ፍላጎቱም ሆነ ብቃቱም የለውም። ይህንን በዐማራው ላይ የተፈጸመውንና እየተፈጸመ ያለውን ሰቆቃ እንዳይቀጥል ማድረግ የሚችለው ማንም ሳይሆን ዐማራው እራሱ ነው። ለዚያም እራሱን በሁለንተናዊ መንገድ ማደራጀትና ጠንክሮ በመገኘት የኅልውናውን ለማስከበር ከመደራጀት አልፎ ግፍ የሠሩበትን ቡድኖችና ግለሰቦ ለፍትሕ ለማቅረብ ሞረሽ ወገኔ የዐማራ ድርጅት እያደረገ ያለውን ትግል መደገፍ ይጠበቅበታል።
(ሞረሽ ወገኔ)